አምስቱ ስጦታዎች
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ የዋጃት ቤተክርስቲያን የእርሱ አካል መሆንዋን ማሰብ ነፍስን በመለኮታዊ ሐሴት እና ውስጥን በሚያረሰርስ እርካታ ይሞላል፡፡ አማኝ በዚያች የክርስቶስ አካል ውስጥ ብልት መሆኑን ሲያሰላሰል የሚያገኘው ደስታ እጅግ ከፍ ያለ ከመሆኑም በላይ ማንም ከዚያ የብልትነት ስፍራ ሊያወጣው የማይችል ስለመሆኑ ማሰብም በጣም ያስደንቀዋል፡፡ ራስ ከሆነው ከክርስቶስ ዘንድም የሚያገኘውን መንፈሳዊ መግቦት በደስታ ይቀበላል፡፡
ከተመሠረተች ጀምሮ ከምድር እስከምትወሰድበት ጊዜ ድረስ በዓለም ሁሉ ያሉ አማኞች የሚገኙባት የክርስቶስ አካል የሆነች ቤተክርስቲያን አንዲት ናት፡፡ ያቺ አንድ አካል አሁንም ቢሆን አለች፡፡ በእርስዋም ውስጥ የሚገኝ እያንዳንዱ አማኝ ብልት በመሆኑ በዚያች አካል ውስጥ አንዳች ሥራ ወይም አገልግሎት ይኖረዋል፡፡ ያንንም ሥራ ወይም አገልግሎት የሚያከናውነው ደግሞ ከጌታ በተሰጠው ጸጋ መሠረት ነው፡፡ ስለሆነም የጸጋ ስጦታን በተመለከተ የእግዚአብሔር ቃል የሚያስተምረውን እውነት መረዳት ከጌታ የተቀበለውን አገልግሎት ለመፈጸም ለተነሳሳ አማኝ ሁሉ በእጅጉ ያስፈልገዋል፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ጸጋ ስጦታዎች የሚያስተምረውን ሁሉ በተገቢው ሁኔታ ማወቅ የብዙ አማኞች ፍላጐት እንደሆነ ይታያል፡፡ ይህም ፍላጐት የተቀደሰ መነሻ እስካለው ድረስ በጸጋ ስጦታዎች ዙሪያ ለሚነሱ ጥያቄዎች ሁሉ የሚያሳርፉ መልሶች ከመጽሐፍ ቅዱስ ይገኛሉ፤ የጸጋ ስጦታዎች ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በሮሜ12፡6-8፤ በ1ቆሮ12፡4-11፤ በ1ቆሮ12፡27-31፤ በኤፌ4፡7-13፤ በ1ጴጥ4፡10-11 ላይ በዝርዝር ተመዝገበው እናገኛለን፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ በቤተክርስቲያን የሚከናወኑ አገልግሎቶች ሁሉ ያለምንም መደነጋገር ይከናወኑ ዘንድ የጸጋ ስጦታዎችን በተመለከተ ሰፊ የቅዱሳት መጻሕፍት ንባባትን ትቶልናል፡፡ ጌታ ቢፈቅድ ወደ ፊት ሁሉንም የምንዳስስ ሲሆን በዚህ ጽሑፋችን ግን ከእነዚህ ንባቦች መካከል በኤፌ4፡7-13 ያለውን መመልከት እንጀምራለን፡፡
«ነገር ግን እንደ ክርሰቶስ ስጦታ መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጠን» (ቊ.7)
ይህ ቃል ለአማኞች በየግል ስለሚሰጥ የጸጋ ስጦታ ይናገራል፡፡ ከዚህ ንባብ በፊት ባሉ ቊጥሮች ስለ አንድ አካል እና ከዚያ አካል ጋር ስለተያያዙ ነገሮች ማለትም ስለ አንድ ተስፋ፣ ስለ አንድ መንፈስ፣ ስለ አንድ ጌታ፣ ስለ አንድ ሃይማኖት (እምነት)፣ ስለአንዲት ጥምቀትና ስለ አንድ አምላክ እናነባለን (ከቊ.4-6)፡፡ ይህም አማኞች እያንዳንዳችን በብልትነት የምንገኝባት የመላዋን ቤተክርስቲያን ገጽታ ያመለክታል፡፡ ከዚያም ሐዋርያው በዚያች አንድ አካል ውስጥ የምንገኝ እያንዳንዳችንን በተመለከተ የጌታ ሐሳብ ምን እንደሆነ ወደ መግለጽ ይመጣል፡፡ በጥቅሉ ስለ አንድ አካል (ስለ መላዋ ቤተክርስቲያን) ከተናገረ በኋላ በመቀጠል ስለእያንዳንዳችን መናገር ይጀምራል፡፡ «ነገር ግን እንደ ክርስቶስ ስጦታ መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጠን» ይላል፡፡ ስለሆነም ቤተክርስቲያን የክርስቶስ አንድ አካል ከመሆንዋ አንጻር እና አንድ ተስፋ፣ አንድ መንፈስ፣ አንድ ጌታ፣ አንድ እምነት፣ አንዲት ጥምቀት፣ አንድ አምላክ የሁሉም አባት ያለን ብንሆንም በየግል ስንታይ ደግሞ እያንዳንዳችን የተለያየ የጸጋ ስጦታ አለን፤ የምንለያየው በሌላ በምንም ሳይሆን ለእያንዳንዳችን በተሰጠን ጸጋ ብቻ ነው፤ ይህን በተመለከተ በሮሜ12፡4 «የብልቶች ሥራ አንድ እንዳይደለ» ስናነብ በዚሁ በኤፌ.4 በቊ.6 ላይ «እንደተሰጠንም ጸጋ ልዩ ልዩ ስጦታ አለን» የሚል እናነባለን፡፡ በ1ቆሮ.12፡4-6 ባለው ክፍል ደግሞ «የጸጋ ስጦታ ልዩ ልዩ ነው፤ መንፈስ ግን አንድ ነው፤ አገልግሎት ልዩ ልዩ ነው፤ ጌታም አንድ ነው፤ አሠራር ልዩ ልዩ ነው፤ ሁሉን በሁሉ የሚያደርግ እግዚአብሔር ግን አንድ ነው» ይላል፡፡ መለያየት በሌለባት በአንዲት የክርስቶስ አካል ውስጥ በእያንዳንዱ አማኝ መካከል የምናየው ልዩነት የእምነት ወይም የትምህርት ወይም የአመለካከት ልዩነት ሳይሆን ከጌታ በተሰጠን የጸጋ ስጦታ ብቻ የሚሆን ልዩነት እንደሆነ እጅግ ውብ ከሆኑት ከእነዚህ የቅዱሳት መጻሕፍት ንባቦች እንማራለን፡፡ ይህ ከስጦታዎች መካከል ብዙዎች እንዲኖራቸው በሚፈልጉት በአንድ የሆነ የጸጋ ስጦታ ተገልጦ ለመታየት ከሚደረገው የዘመናችን ሁኔታ ጋር ሲተያይ እንዴት የተለየ ነው!
የጸጋ ስጦታዎች ለእያንዳንዳችን የተሰጡት በእያንዳንዳችን ፍላጎት መሠረት አይደለም፤ ቃሉ «እንደ ክርስቶስ ስጦታ መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጠን» ይላል፡፡ «እንደ ክርስቶስ ስጦታ መጠን» የሚለው ቃልም ለእያንዳንዱ አማኝ የሚሰጠው የጸጋ ስጦታ የሚወሰነው በክርስቶስ ብቻ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ጸጋውን የሚሰጠንም ሆነ በጉባኤ መካከል በዚያ በሰጠን ጸጋ የሚገልጠን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ እኛ እንዲኖረን የምንፈልገውን ወይም በሌላ ሰው ላይ ያየንውንና ለእኛ እንዲሆን የተመኘነውን ስጦታ ጠቅሰን በጸሎት እስከመጠየቅ መድረስ ይህን እውነታ አለመረዳት ወይም በእጅጉ ቸል ማለት ነው፡፡ ጌታ ስጦታዎችን የሚሰጠው በአማኞች ሁኔታ ወይም የግል ፍላጎት ላይ ተመሥርቶ ሳይሆን በራሱ መሻትና ፈቃድ ላይ ብቻ ተመሥርቶ ነው፡፡ ስጦታውም የጸጋ ስጦታ እንደመሆኑ መጠን በእኛ ሁኔታ ላይ ተመሥርቶ ሊሰጠን አይችልም፡፡ በመሆኑም እኛ ማድረግ ያለብን ከመጀመሪያው ጀምሮ ከጌታ ዘንድ የሚቀርብልንን ጥሪ ከእምነት በሚነሣ መታዘዝ እየተቀበልን እንደቃሉ መኖር ብቻ ነው፡፡ ከዚያም በጊዜ ውስጥ እርሱ ራሱ ባስቀመጠን የብልትነት ስፍራችን የተሰጠንን ሥራ እንሠራ ዘንድ የሚያስፈልገውን ጸጋ ይሰጠናል፤ በራሱ ጊዜም በቤተክርስቲያን መካከል በሰጠን ጸጋ ይገልጠናል፡፡ ይህንን ማጤን «ጌታን የማገለግልበትን ጸጋ እንዴት ላውቅ እችላለሁ?» ለሚለው የብዙዎች ጥያቄ መልስ ሊሆን ይችላል፡፡ ጌታ እርሱን የሚያገለግሉበትን ጸጋ እንደሚሰጥ እና በራሱ ጊዜ በዚያ ጸጋ እንደሚገልጥ ማመን የእኔ ጸጋ የትኛው ይሆን? ብሎ ከመጨነቅ ይልቅ ጌታን በታማኝነት ወደመጠበቅ ይወስደናል፡፡ ከሰዎች በሚገኝ ሹመት ለማገልገል ፈቃድ እናገኝ ዘንድ አለቆችን ወይም መሪዎችን ደጅ ከመጥናት ይልቅ ጌታ በራሱ ፈቃድና በራሱ መንገድ እንዲያሰማራን ራሳችንን ለእርሱ እንተዋለን፡፡
ስለዚህ፡- ወደላይ በወጣ ጊዜ ምርኮን ማረከ ለሰዎችም ስጦታን ሰጠ (ቊ.8)
የስጦታዎቹ ባለቤትም ሆነ የስጦታዎቹ ምንጭ ጌታ ኢየሱስ ነው፡፡ ለሰዎች ከሰጣቸው ስጦታዎች አንጻር የእርሱ ማንነት የተገለጠውም ወደ ላይ በወጣ ጊዜ ምርኮን የማረከ ድል አድራጊ ጌታ ሆኖ ነው፡፡ ይህም በመዝ.68፡18 ላይ አስቀድሞ ስለመሢሕ የተነገረ ቃል ነበር፡፡ በዚያ ስፍራ «ወደ ላይ ዓረግህ፤ ምርኮን ማረክህ፤ ስጦታንም ለሰዎች ሰጠህ» የሚል ቃል እናነባለን፡፡ ጳውሎስ በኤፌ.4፡8 ላይ የጠቀሰውም ይህንኑ ቃል ነው፤ በዚህ ቃል ውስጥ «ወደ ላይ በወጣ ጊዜ» የሚለው ጌታችን ከሞት ከተነሣ በኋላ በ40ኛው ቀን ወደ ላይ ወደ አባቱ ያረገበትን ጊዜ ያመለክታል፡፡ ይህም የሚታወቀው ከቊ.9-10 ላይ «ወደ ምድር ታችኛው ክፍል ደግሞ ወረደ ማለት ካልሆነ ይህ ወጣ ማለትስ ምን ማለት ነው? ይህ የወረደው ሁሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ደግሞ ያው ነው» ተብሎ በተጻፈው ቃል ነው፡፡
ጌታ ወደ ላይ በወጣ ጊዜም ምርኮን የማረከ ድል አድራጊ ሆኖ ነበር የወጣው፡፡ ምርኮውም ሌላ ምንም ሳይሆን በጨለማ ሥልጣን ሥር ሆኖ በሞት ፍርሃት ተይዞ በዲያብሎስ እየተገዛ ይኖር የነበረ ሕዝብ ነው፡፡ ጌታ ኢየሱስ ሞትን ድል አድርጎ በተነሣ ጊዜ ዲያብሎስ ሰዎችን የሚያስፈራራበት የሞት ኃይል የተሻረ በመሆኑ ብዙ ምርኮን ሊያገኝ ችሏል፡፡ ይህም በኋላ የትንሣኤው ምስክሮች በሰበኩት ወንጌል ብዙዎች ወደ ኢየሱስ በመፍለሳቸው ተረጋግጧል፡፡ እንዲህ ያለው ብዙ ምርኮን የማረከ ድል አድራጊ ደግሞ ለሕዝቡ የሚሰጠው ብዙ ነገር ይኖረዋል፤ በመሆኑም ኢየሱስ ወደ ላይ ከወጣና በአባቱ ቀኝ በክብር ከተቀመጠ በኋላ ለሰዎች ስጦታን ሊሰጥ ችሏል፡፡
«እርሱም አንዳንዶቹ ሐዋርያት፣ ሌሎቹም ነቢያት፣ ሌሎቹም ወንጌልን ሰባኪዎች ሌሎቹም እረኞችና አስተማሪዎች እንዲሆኑ ሰጠ» (ኤፌ.4፡11)፡፡
የቤተክርስቲያን ራስ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ የስጦታዎች ባለቤት እንደመሆኑ መጠን ለሰዎች ስጦታን ይሰጣል፤ እርሱ ለአማኞች በየግላቸው የሚያገለግሉበትን ጸጋ ይሰጣል፤ እንዲሁም ስጦታዎችን ለእያንዳንዱ አማኝ ከመስጠት ባሻገር የጸጋ ስጦታ የሰጣቸውን ሰዎችንም ለቤተክርስቲያን ስጦታ አድርጎ ይሰጣል፡፡ በዚህ በቊ.11 ላይ የተዘረዘሩት አምስቱ ስጦታዎችም ወደ ላይ ያረገውና ራስ የሆነው ክርስቶስ ለቤተክርስቲያን የሰጣቸው ሰዎች ናቸው፡፡ ሐዋርያት፣ ነቢያት፣ ወንጌል ሰባኪዎች፣ እረኞችና አስተማሪዎች ሲል በፊት በየግላቸው የሐዋርያነት፣ የነቢይነት፣ የወንጌል ሰባኪነት፣ የእረኝነትና የአስተማሪነት ስጦታዎችን ከክርስቶስ የተቀበሉ ሰዎችን ያመለክታል፤ ከዚያ በኋላ ኢየሱስ እነዚህን ሰዎች ራሳቸውን ለቤተክርስቲያን ሰጥቷል፡፡
እነዚህ አምስት ስጦታዎች ለመላይቱ ቤተክርስቲያን የተሰጡት የስጦታዎቹ ባለቤት በሆነው በራሱ በጌታ ኢየሱስ ብቻ መሆኑን በትኩረት ማስተዋል ይገባል፡፡ ይሁንና ይህን ካለማስተዋል የተነሣ እነዚህ ስጦታዎች የቤተክርስቲያን ባለሥልጣናት የሚባሉ ሰዎች የሚሾሟቸው አገልጋዮች ተደርገው በብዙዎች ዘንድ ይታሰባሉ፤ እንደዚሁም እነዚህ አምስት ስጦታዎች ልክ በሌሎች የሥራ መስኮች እንደሚሰማሩ ሰዎች ከተለያዩ የቲዎሎጂ ተቋማት የተመረቁና በሐዋርያነት፣ በነቢይነት፣ በወንጌላዊነት፣ በእረኝነት (በፓስተርነት) እና በአስተማሪነት ሥራ ተቀጥረው በሠራተኝነት የሚያገለግሉ ሰዎችን እንዲያመለክቱም ተደርገዋል፤ ይህም በየስፍራው ከሚገኙ ቅርንጫፍ አጥቢያዎች ለወንጌላዊነትም ሆነ ለፓ¬ስተርነት ሰዎች ከተመለመሉ በኋላ ከበላይ አካላት በወጡ መመዘኛዎች ተወዳድረው ያለፉት ወደ ማሠልጠኛ ተቋማት እንዲገቡ የሚደረጉበት፣ እንዲሁም ከዚያ በኋላ እንደ አንድ የሥራ መስክ (ፊልድ) በወንጌላዊነት ወይም በ¬ስተርነት የሚመረቁበትና በዚያም ባገኙት ዲፕሎማ (ዲግሪ) መሠረት በተለያዩ ወረዳዎች ከተሞችና አጥቢያዎች በማዕርጋቸው ተሹመው የሚመደቡበት አሠራር እነዚህ አምስቱ ስጦታዎች ጌታ ለቤተክርስቲያን የሚሰጣቸው ስጦታዎች መሆናቸውን በተግባር የሚክድ አሠራር ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ እንደማንኛውም የቢሮ ሠራተኛ በአንድ ወቅት ወንጌላዊ የነበረ ሰው በዕድገት በሌላ ጊዜ ፓስተር ወይም ምክትል ¬ፓስተር ወይም ደግሞ እንደ ሁኔታው እየታየ ሐዋርያም ተብሎ እየተሾመ በሥልጣን ከፍ የሚደረግበት ከዚህም ጋር የሚያገኛቸው ጥቅማ ጥቅሞች (ነውረኛ ረቦች) የሚያድጉበት ወይም ደግሞ በተቃራኒው በአንድ ወቅት ፓ¬ስተር የነበረው ተሽሮ በምትኩ ከበላይ አካላት በደብዳቤ ሌላ የሚሾምበት አሠራር በባሕርዩ ፍጹም ዓለማዊ ከመሆኑም ሌላ በሰማይ ያለው የቤተክርስቲያን ራስ እርሱ ራሱ የሚያስፈልጉንን የቃሉን አገልጋዮች እንደሚሰጥ ካለማመን ወይም የእርሱን ስጦታ ወደ ጐን ከመተው የሚመጣ አሠራር ነው፡፡ ነገር ግን በሰማይ ያለው የቤተክርስቲያን ራስ ጌታ ኢየሱስ ዛሬም አካሉ ለምትሆን ቤተክርስቲያን የሚያስፈልጓትን ሰዎች እንደሚሰጣት የሚያምኑ ሁሉ እነዚህ ሰዎች በመካከላቸው በሂደት በጸጋቸው ሲገለጡና ጌታም በድንቅ ሲጠቀምባቸው ያያሉ፡፡
ጌታ ለቤተክርስቲያኑ ስለሚሰጣቸው ስጦታዎች በተለይም ስለ 5ቱ ስጦታዎች በጥቅሉ ይህንን ያህል ካልን አሁን ደግሞ አምስቱን ስጦታዎች እያንዳንዳቸውን በዝርዝር ማየት እንጀምራለን፡፡ አንባቢውም አሁን በተለምዶ እየተሠራበት ካለው ሥርዓት አንጻር ሳይሆን የእግዚአብሔር ቃል ከሚናገረው እውነት አንጻር ብቻ ስለ እነዚህ ስጦታዎች የሚያነበውን ሁሉ በትዕግሥት እየመረመረ እንዲያጠና በፍቅር ይጠየቃል፡፡
ሐዋርያት